Thursday, May 9, 2013

አቡነ ቀውስጦስ

   
      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን ::

እንኳን ታላቁ ኢትዮጵያዊው አባት አቡነ ቀውስጦስ በዓለ ልደት አደረሳችሁ
በቤተክርስቲያናችን ግንቦት 1 ታስበው ከሚውሉ ታላላቅ አባቶች መካከል ኢትዮጵያዊው አባት አቡነ ቀውስጦስ አንዱ ናቸው፡፡ ለመሆኑ አቡነ ቀውስጦስ ማን ናቸው? ምንስ ቃል ኪዳን ተሰጣቸው? ባጭሩ እንመልከት ምልጃና በረከታቸው ይደርብን አሜን
ጻድቀ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ የተወለዱት በሸዋ ክፍለ ሀገር በወግዳና ቡልጋ ውስጥ ሲሆን አባታቸው ገላውዲዮስ እናታቸው እምጽዮን ይባላሉ፡፡ የጻድቁ የአቡነ ተክለሃይማት እናት እግዚአኃሪያ እና እምነጽዮን ታናሽና ታላቅ እህትማማቾች ናቸው፡፡ ገላውዴዎሰ እና እምነጽዮን እግዚአብሔር የተባረከ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ለዓመታት በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስዕል ፊት ሲጸልዩና ሲለምኑ የእመቤታችንም ስዕል አፍ አውጥቶ አናገረቻቸው እንዲህም አለቻቸው፡፡ ‹‹አንድ ልጅ አስቀድማችሁ ትወልዳላችሁ የሚወለደውም እኔ በተወለድኩበት ግንቦት 1 ቀን ሲሆን እረፍቱም በእኔ የእረፍት ቀን ጥር 21 ነው፡፡ እሱም የሰማያዊ ንጉስ ጭፍራ ይሆናል፡፡ ››አለቻቸው በተገባላቸው ቃል መሰረት ግንቦት 1 ቀን ጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ ተወለዱ፡፡
ጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ የዚህን ዓለም ተድላ ደስታና ጣዕም ንቀው ፈለገ ሐዋርያትን ተከትለው በሸዋ፤ በከፋና፤ በጅማ ዞረው የጌታችን የመድሐኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል በማስተማር ከአረማውያን ነገስታትና ባላባቶች የሚደርስባቸውን መከራና እንግልት በመታገስ በተጋድሎ ጸንተው ብዙውን ሕዝብ ከአምልኮት ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር ከኃጢያት ወደ ጽድቅ መልሰዋል፡፡በተለይ በሸዋ ክፍለ ሀገር ፈንታሌ ተራራ ላይ ሠረቲ ለምትባል ጠንቋይ እየተላላኩ ህዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ አራት መቶ ሰባ ሺህ ሦስት መቶ አጋንንትን እንደ ነብዩ ኤልያስ በጸሎታቸው ከሰማይ እሳት አውርደው ተራራውን ደምስሰው አጋንንቱን አቃጥለዋል፡፡ሕዝቡንም ለጣዖትና ለጠንቋይ ከመገዛት አድነውታል፡፡
ጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ በብዙ ተጋድሎ ሲኖሩ በሰማዕትነት ያርፍ ዘንድ ስለ እግዚአብሔር መንግስትና ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚተጉ እንጂ የዚህን ዓለም መንግሰት ሀብትና ሥልጣን የማይሹ እውነተኛ መናኝ ነበሩና የታናሽ ወንድማቸው የአጼ ይኩኖ አምላክ ልጅ አጼ አምደጽዮን የአባቱን እቁባት በማፈግባቱ ‹‹ይህንን ልታደርግ አይገባም››ብለው እንደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ (ማር 7፡14-29) ቢገስጹት 11 አሽከሮችን በሌሊት ልኮ ከበዮ ወደ እንሳሮ ሀገር ካስወሰዳቸው በኃላ ኮሶ አረህ ከሚባለው አፋፍ ላይ እኩለ ሌሊት በጦር ጎናቸውን አስወግቶ ደማቸውን አፈሰሰሰ፡፡ደማቸውም እስከታላቁ ወንዝ ጅማ ድረስ ሆነ፡፡የፈሰሰው ደማቸውም ቀይ ብርሃን ሲሆን የሌሊቱ ጨለማ ከጸሐይ ሰባት እጅ የሚበልጥ ብርሃን በአውራጃውቹ ሁሉ ታየ፡፡በዚህ የተነሳ እስከ ዛሬ ድረስ ሀገሩ ቀን ተብሎ ይጠራል፡፡
በብዙ ተጋድሎ ከቆዩ በኃላ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ሳትለይ በስቃይ ላይ ላሉም በዘመናቸው ሁሉ ስለነበራቸው ተጋድሎ ንጽህናና ምናኔ ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ድንግል ማርያምና ቅዱሳኑኑ እና መልአክታኑን አስከትሎ ቃል ኪዳን ሊሰጣቸው መጣ፡፡ እንዲህም አላቸው እኔ ለአንተ ዓይን ያላውን ጆሮ ያልሰማውን መንግስተ ሰማያትን አዘጋጀውልህ በዚያም ታላቅ ወንበር ታገኛለን በዘመንህ ስላሳለፍካቸው ክርስቲያናዊ ተጋድሎህ 7 የብርሃን አክሊላትን አዘጋጀውልህ 2ቱ እንደ እነ ነብዩ ኤልያስና ነብዩ ሳሙኤል ለሆነ ንጽህናህ 2ቱ እንደ እነ ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ለሆነ የወንጌል ስብከትህ 2ቱእንደ እነ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ቅዱስ ፊቅጦር በትዕግስት ሥለተጋደልክ አንዱ ስለ ልብ ርህራሄ ነው አላቸው፡፡
እንዲሁም ስለ እኔ ምስክርነት የሞትክባት ምድር እንደ ዳዊት ሀገር እንደ ኢየሩሳሌም ትሁንልህ ወደ እርሷ የሄደውንም ሁሉ ወደ ኢየሩሳሌም ወደ መቃብሬ ጎሎጎታ እንደ ሄደ እቆጥርለታለሁ፡፡ ብዙ ኃጢያት የሰራ ሰው ንሰሐ ገብቶ በዚህች ሀገር በስምህ ጥቂት ምጽዋት ቢሰጥ እኔ ኃጢያቱን እደመስስለታለሁ፡፡በጠበልህም ቢጠመቅ በደሉን አጠፋለታለሁ፡፡ደምህ በምድሪቷ ፈሷልና፡፡
በእረፍት ዕለትህ ለቤተክርስቲያን ለቅዱስ ቁርባን ስንዴ ወይንና ዕጣን ያቀረበ ኃጢያት የሰራ ቢሆን ንሰሐ ቢገባ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እንደተቀበለ ንጹህ ሰው አደርገዋለው፡፡ ለስምህ መታሰቢያ በታነጸው ቤተ መቅደስ በንጹህና ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን የሚቀበል ሰው ራሱን ቤተሰቡን እና ባልጀሮቹን ያድናል፡፡
ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ ይህንን ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው ወደ ሰማይ አረገ፡፡ቅዱሳን መልአክትም ነፍሳቸውን ከሥጋቸው በክብር ለዩ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም በሰማይ መካከል ሆና ነፍሳቸውን በፈገግታ ተቀበለች ፡፡
የእረፍታቸውም እለት እመቤታችን ባረፈችበት ጥር 21 ቀን በመሆኑ እመቤታችንም መታሰቢያህን ለሚያደርጉ ሁሉ በልጄ በረከት እባርካቸዋለሁ ብላ ቃል ኪዳን ገባችላቸው፡፡ ጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ ባረፉበት ዕለትም ብዙዎች ከደዌአቸው በረከትና ፈውስ አግኝተዋል፡፡ አሁንም ድረስ ደማቸው በፈሰሰበትና አጽማቸው ባረፈበት ቦታ ብዙ ምዕመናን ፈውሰ ሥጋ ፈውሰ ነፍስ እያገኙበት ነው፡፡የጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ በዓል ግንቦት 1 ቀን የተወለዱበት ጥር 21 ቀን ያረፉበትና ቃል ኪዳን የተቀበሉበትን በማዘከር በታላቅ ድምቀት በገዳሙ ይከበራሉ፡፡
ገዳመ ቀውስጦስ የሚገኘው ከአዲስ አባባ በስተሰሜን 120 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ሲሆን ወደ ደብረ ሊባኖስ በሚወስደው መንገድ ሙከጡሪ ከተማ ሲደርሱ ወደ ቀኝ በመታጠፍ ሚቴና በዩ በሚባለው አካባቢ ልዩ ስሙ መገንጠያ ከሚባል ቦታ ነው ውይም ወደ ጅሩ አርሴማ ቅድስት ሲሄዱ ወርደው ከአቡነ ቀውስጦስ ተባርከው መሄድ ይችላሉ ፡፡መንገዱ እዚያው ገዳሙ ድረስ መኪና የሚያስገባ በመሆኑ ምዕመናን ቦታው ድረስ በመሄድ ከጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ በረከት ማግኘት የምትችሉ መሆኑን እገልጻለን፡፡የጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ ረድኤትና በረከት ጸሎት ዘወትር አይለየን አሜን ፡፡ አባት ሆይ በረከትህን እናገኝ ዘንድ ባርከን!!!
ምንጭ፡-ገድለ አቡነ ቀውስጦስ

ጸሀፊ ገዛኸኝ ፈንታሁን

No comments:

Post a Comment