Friday, May 31, 2013

ፃዲቁ አቡነ በግዑ


          በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
 የቅዱሳን ተጋድሎ ማውሳት ለመንፈሳዊነታችን ታላቅ አስተዋፅኦ አለው:: በየዕለቱ የምንሰማው የቅዱሳን ህይወትና ታሪክ እነርሱ ወደ ተጋደሉበት የቅድስና መንገድ የሚመራንና ለተሻለ የመንፈሳዊ ህይወት የምንጒዝበት ትልቅ ድልድይ ነው::

የጻድቅ ሰው ጸሎት በስራዋ እጅግ ሐይል ታደርጋለች:: ያዕቆብ 5 : 
 ጻድቁ አቡነ በግዑን ላስተዋውቆ በቤተክርስቲያናችን ታስበው ከሚውሉ ቅዱሳን መካከል ጻድቁ አቡነ በግዑ አንዱ ናቸው:: ለመሆኑ አቡነ በግዑ ማን ናቸው? ምንስ ተጋድሎ አደረጉ? ምንስ ቃል ኪዳን ተሰጣቸው? የሚለውን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እንመልከት መልካም ንባብ
ፃዲቁ አባታችን አቡነ በግዑ ቀድሞ በክፉ ስራ በኋላም በመልካም ተጋድሎ ፈጣሪው እግዚአብሔርን አገልግሏል፡፡ መጀመሪያ እንደ ሽፍታ በማታለል ከኖረ በኋላ ግን በብዙ ጾምና ፀሎት ወደ እግዚአብሔር ተመለሰ፣ ሲዘርፍና ሲቀማ ኖረ፣ ባማረ ልብሶች ሲያጌጥ ኖረ በኋላ ግን ጽድቅን እንደልብስ ለበሰ በጉልምስና ጊዜው ብርቱ ጠንካራ ስለነበረ ወደ እርሱ መቅረብ የሚችል አልነበረም፡፡ ብርቱ ጠንካራ ስለነበረ ወደ እርሱ መቅረብ የሚችል አልነበረም፡፡ የሀገሩ ሰዎች ሁሉ ይፈሩታል፡፡ በሰዎች ሁሉ ዘንድ የታወቀ ነበረ፡፡
አባታችን አቡነ በግዑ አስቀድሞ በስም ክርስቲያን ነበረ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ቁርባን ሊቀበል ከህዝቡ ጋር ወደ ቤተክርስቲያን ሄደ፡፡ ካህኑ ባየው ጊዜ ከመንገድ አስገልሎ የህይወት ዘመንህን ሁሉ በከንቱ አሳለፍክ ዛሬ ስማ ልንገርህ በዘመን ፍፃሜ እግዚአብሔር ይጎበኝሃል፣ መንፈስ ቅዱስ ያድርብሃል ፍፁም መነኩሴ ትሆናለህ ከቤተሰቦችህም ተለይተህ ከፍ ወደ አለ ቤተክርስቲያን ትደርሳለህ በጾም በፀሎት በብዙ መከራም በዚያ ትኖራለህ አለው፡፡ ይህንንም በሰማ ጊዜ በእውነት ይደረግልኝ ይሆን? እያለ አሰበ የክርስቶስን ክቡር ስጋው ቅዱስ ደሙን ተቀብሎ ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡
ከዚያች ዕለት ጀምሮ እስከ መቼ በስንፍናዬ እኖራለሁ እስከ መቼስ የነፍሴን መዳኛ ሳላስብ እኖራለሁ እያለ ከዘመዶቹ ተለይቶ ከሀገር ወጥቶ ሄደ ኢዮ 40፡4 ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን ገባ፡፡ ከመነኮሳት ማህበር ገብቶ እያገለገለ ከአንድ አረጋዊ መነኩሴ ጋር ኖረ፡፡ በጸም በፀሎትተወስኖ እግዚአብሔርን እያገለገለ በትንሽ በዓት ብቻውን ሆነ፡፡ በጾም ወራት ይኸውም በአብይ ጾም በህብስትና በውሃ ብቻ መጾም ጀመረ፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለበት ዕለት አርብ በህማማት ሳምንት ሁሉ ከንቱ ነው ብላሽ ነው የዚህ ዓለም አኗኗር ኃላፊ ነው የሚል የመጽሐፍ ቃል ሲነበብ ሰማ እንባው እንደውሃ እስኪወርድ ድረስ መሪር ልቅሶ አለቀሰ 1ዮሐ 2፡15 ከዚያች ቀን ጀምሮ ስጋዊ ስራን ተወ፡፡ ምግቡንም የዱር ዛፍ ፍሬና ቅጠል አድርጎ በተጋድሎ ውሃ ሳይጠጣ ኖረ፡፡
አበምኔቱና ቅዱሳን መነኮሳት ያለውሃ በመኖሩ የእግዚአብሔር ቸርነቱን አደነቁ፡፡ አባታችን አቡነ በግዑ አበምኔቱን አስጠርቶ ከበአቴ አልወጣም ብሎ በፈቃዱ ሁለት እጁንና ሁለት እግሩን በብረት ሰንሰለት አሰረ፡፡ አበምኔቱም ፈቀዱለት ባአቱንም በውስጥም በውጭም እጅ የሚያስገባ ትንሽ መስኮት በመተው በጭቃ መረጉት ይህም ለምግብ የሚሆን ቅጠል የሜዳ ጐመንና የዱር ፍሬ የሚገባበት ነው፡፡ አባታችን አቡነ በግዑ አፉን በጨርቅ አሰረ፡፡ በጾም በፀሎት ከእንባ ጋር ተጋድሎውን አደረገ፡፡ አበምኔቱ በትንሽ ልጅ የሚልኩለትን ቅጠል የኃጢአቱን ክርፋት እያሰበ ያለውሃ አብስሎ እስኪከረፋ ከአጠገቡ ያስቀምጠዋል ሽታውም ከአይነ ምድር ይከፋል፡፡ በጾመ በሶስተኛው ቀን ያን የከረፋ ቅጠል ይበላል በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓል ቀን ከበአቱ ወጥቶ በዮርዳኖስ ተጠመቀ፣ ቁርባንም ተቀብሎ አስቀድሞ እንደነበረው ወደ በአቱ ገባ፡፡ ከዚህ በኋላ ግን አልዘጋውም ለበአቱ ደጃፍ መዝጊያ አሰራ ቁርባን መቀበል አላቋረጠም፡፡
የአባታችን የአቡነ በግዑ ተጋድሎው ከውሃ ተከልክሎ የተቀበለው መከራ በሀገሩ ሰዎች ዘንድ ተሰማ፡፡ የሀገሪቱ ንጉስም በፀሎት አስበኝ ብሎ በመልክተኛ ልብስ ላከ ፃዲቁ አባታችን እንዲህ አለው የእግዚአብሔር ቸርነት ከአንተ ጋር ይሁን ይሄንን ልብስ አልቀበልም ለአንተም ለእኔም ወደ እግዚአብሔር እማልድ ዘንድ በዚህ ልብስ ፈንታ እጣን ላክልኝ አለው፡፡ ንጉሱም እንደተባለው አደረገ አባታችንም ዕጣኑን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ሰጠ፡፡ ምሳ 18 ፡ 12
ፃዲቁ አባት አቡነ በግዑ ውሃ መጠጣት ከተወ አምስት ዓመት ሆነው መቀመጥና በጎኑም መሬት ላይ መተኛት ተሳነው ስጋው አልቋልና፡፡ ከንፈሮቹም ከውሃ ጥም የተነሳ ደረቁ፣ ምላሱም ተጣበቀ፣ አይኖቹም በእንባ ደፈረሱ፣ አፍንጫውም ቆሰለ መገለ፣ መሄድም ተሳነው ሲወጣና ሲገባ በሁለቱ እጆቹና እግሮቹ ይድሃል፡፡ ቁርባን ሲቀበል ሁለት መነኮሳት አድርሰው ይመልሱታል፡፡ ይህን ጽኑ መከራ ከተቀበለ በኋላ ነፍሱን እንዲወስድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ በምሳሌ አስረዳው ከሞት ወደ ህይወት ትሻገር ዘንድ መከራውን ረኃቡንና ጥሙን ታገስ አለው፡፡ ያዕ 1 ፡ 12
አባታችን አቡነ በግዑ ይህን ሁሉ ተጋድሎ በእግዚአብሔር ኃይል አደረገ፣ ለሰባት አመት ውሃ ሳይጠጣ ኖረ፡፡ ከሰባት ዓመት በኋላ ከብዙ ረኃብና ጥም የተነሳ በጣም ታመመ፡፡ መናገርም ተሳነው፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን ጎበኘ፡፡ የኃጥአን መኖሪያቸውን ተመለከተ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር አዕላፍ ቅዱሳንን ይዞ መጥቶ ስምህን ለጠራ፣ መታሰቢያህን ላደረገ፣ ወደ ተቀበርክበት ቦታ ሄዶ ለተሳለመ፣ በበአልህ ቀን ምጽዋት ለሰጠ እስከ ሰባት ትውልድ እምርልሃለሁ አለው ዳግመኛ በፀሎትህ አምኖ መልካም ስራ የሰራ የገድልህን መጽሐፍ የሰማ ሁሉ የእሳትን ባህር በግልጽ ይለፍ ብሎ ቃለ ኪዳን ገባላት፡፡
የእግዚአብሔር ሰው አቡነ በግዑ በአባታችን አቡነ ኢየሱስ ሞዓ እጅ ምንኩስናን ተቀበለ፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዓን ዛሬ ግን ደክሜያለሁ መናገር ተስኖኛል፡፡ ነፍሴ ከስጋዬ መለያዋ ጊዜው ቀርቧል፡፡ መቃብር አስቆፍርልኝ አሁን ግን ወደ በዓትህ ተመለስ ብሎ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ አሰናበተው ህመሙ ሲጠናበት አቡነ ኢየሱስ ሞዓ ተመልሰው መጡ፡፡ አቡነ በግዑንም ስለ ጽድቅ ብለህ እስከ ሞት ድረስ ተጋደልክ አሁን ግን ከእጅህም ከእግርህም ይህን የብረት ሰንሰለት እንፍታ አለው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው አቡነ በግዑ ከሞትኩ በኋላ የታሰርኩበትን ሰንሰለት ፍቱት ፈቃድህ ከሆነ አሁን ፍታኝ ብሎ የብረት ሰንሰለቱ ተፈታ፡፡ ጥቂት ደቂቃ እንደቆየ ታህሳስ 27 ቀን አረፈ፡፡ መዝ 115/116 ፡ 6
የአባታችን የአቡነ በግዑ ረዴትና በረከት ይደርብን!!!
 ወስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘበቅዱሳኒሁ ይሴባሕ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ወለዓለም ዓለም አሜን፡፡ ወአሜን ለይኩን ለይኩን፡፡  
ፀሀፊ ገዛኸኝ ፈንታሁን       By gezahagn fantahun

No comments:

Post a Comment