Tuesday, May 26, 2015

አቡነ ዓብየ እግዚእ

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !
  ዕረፍቱ ለአቡነ ዓብየ እግዚእ
ጻድቁ አቡነ ዓብየ እግዚእ ከአባታቸው ያፈቅረነ እግዚእ እና ከእናታቸው ከጽርሐ ቅዱሳን በአልአሜዳ ዘመነ መንግሥት በትግራይ ሀገረ ስብከት: በሀገረ ሰላም ወረዳ ልዩ ስሙ መረታ አሪያ በሚባል ቦታ ተወለዱ። ዕድሚያቸው ለትምህርት በደረሰ ጊዜ ገና በ7 ዓመታቸው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ወደ ምናኔ ገብተው አባ ዘርዓሚካኤል ከተባሉ አባት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንና ሌሎችንም መንፈሳዊ ትምህርቶች ተማሩ።
ጻድቁ አቡነ ዓብየ እግዚእ ለመጀመሪያ ጊዜ ሱባኤ የያዙት አገፋት በሚባል ቦታ ነው። ጸሎታቸውን (ሱባኤያቸውን) ከጨረሱ በኋላ ከዚህ አገፋት ከሚባል ቦታ ወደ ደብረ ዓባይ ገዳም በዝሆን ተጭነው ሄደዋል። እዛም ከቅዱሳን በረከት ተቀብለው እንደገና ወደ ዋልድባ ገዳም በመሄድ በምናኔና በጸሎት ቅዱሳንን ሲያገለግሉ ከቆዩ በኋላ ቦታቸው ዋልድባ እንዳልሆነ ጌታ በራእይ ገለጸላቸው። እሳቸው ግን ቦታውን በጣም ስለወደዱ ከዚህ አልሄድም አሉ። እግዚአብሔር አምላክ ቅዱሳኑንን እንዳያዝኑበት ይጠነቀቃልና ዮናስን ቀስ አድርጎ እንዳስረዳው አባታችንን ደግሞ በተኙበት ጊዜ ቅዱሳን መላእክት መጥተው ለበረከትም እንዲሆን የተኙባት ቦታ ቀርድደው ከነ አፈሩ አንስተው አሁን ገዳማቸው ባለበት ቦታ በመረታ አኖሩዋቸው።
ጻድቁ አቡነ ዓብየ እግዚእ ወደ ኢየሩሳሌም በደመና ሰረገላ ተጭነው፣ በመሄድ የጌታን መቃብርና ጎልጎታን በመሳለም ወደ ሀገራቸው ሲመለሱ እግረ መንገዳቸውን ከአቡነ እንጦንስና ከአቡነ መቃርስ መቃብር አፈራቸውን ለበረከት ይዘው በመምጣት በገዳሙ በትነውታል።
ንዕማን ከቅድስት አገር ኢየሩሳሌም ሁለት የበቅሎ ጭነት አፈር ወደ አገሩ እንደወሰደ፣ እንዲሁም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ከተቀበሩበት መቃብር ከሮም፣ ከደብረ ምጥማቅ ከእመቤታችን ገዳም፣ ከሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ መቃብር፣ ከአክሱም ጽዮንና ከሌሎችም ቅዱሳን መካናት፣ አፈራቸውን ያዙ።
መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል "ገዳምህ ይዘኸው ብትሄድ ለሰውና ለእንስሳ መድኃኒት ይሆንልሃል። ገዳምህ ልዩ ስሙ ተንስሐ በተባለ ቦታ ነው" ብሎ በራእይ ስለነገራቸው ህዳር 20 ቀን በብርሃን ሰረገላ ተጭነው የተቀደሰውን አፈር በትነውታል።
ጻድቁ አቡነ ዓብየ እግዚእ ልዩ ልዩ ተአምራት በእግዚአብሔር ኃይል አድርገዋል። ለምሳሌ ያህል
   1- የጻድቁ አባታችንን የተቀደሰው አፈር ይዘው ሲመጡ መምጣጣታቸውን ያወቁ ተንስሐ በሚባል ገዳም የተቀበሩ ቅዱሳን አባቶች፣ ልክ እንደ አልዓዛር ከመቃብራቸው በመነሳት ጻድቁ አባታችንን ተቀብለዋቸዋል። ጻድቁ አባታችን ዓብየ እግዚእም በብርሃን ሰረገላ ወርደው ባርከዋቸዋል።
    2- አጼ ገብረመስቀልና የመንፈስ ቅዱስ ጓደኛቸው አቡነ ብእሴ እግዚእ የተባሉት አብረው እያሉ ሁለት ሰዎች ሞተው ወደ ቀብር ሲወስዷቸው በስውር በእግዚአብሔር ስም ጸልየው ከሞት አስነስተዋቸዋል። ይህ ተአምር የተደረገው በአክሱም ጽዮን ውስጥ ነው። ይህንን የአቡነ ዓብየ እግዚእ ቅድስና የገለጹት አቡነ ብእሴ እግዚእ ናቸው።
    3- በተጨማሪም ኤልያስ በመጎናጸፊያው ዮርዳኖስን ወንዝ መትቶ ከኤልሳዕ ጋር በደረቅ እንደተሻገሩ እና ሙሴ የኤርትራን ባህር ከፍሎ እስራኤላውያንን እንዳሳለፋቸው ሁሉ ጻድቁ በነበሩበት ወቅት የተከዜን ወንዝ ሞልቶ ብዙ ነጋድያንና አረማውያን ተጨንቀው እያሉ የተከዜን ወንዝ በመባረክ ውሃዉን አቁመው እንዲሻገሩ አድርገዋል።
(ነገ ካልዕ 1:7-10፣ ዘዳ 14:10-30)
ይህንን ድንቅ ተአምር የተመለከቱ ከ 900 በላይ የሚሆኑ እስላሞች: የእግዚአብሔርን ቸርነትና የጻድቁን ድንቅ ሥራ በማድነቅ ወደ አባታችን ዓብየ እግዚእ በመቅረብ ተጠምቀው ወደ ክርስትና እምነት ተመልሰዋል።
ጻድቁ አባታችን አቡነ ዓብየ እግዚእ ኢልክን በተባለ ከመቀሌ 10 ኪሜ ርቀት ላይ በሚገኝ ቦታ ሱባኤ ይዘው ይጸልዩ ነበር። በዚህ ስፍራም በስማቸው በፈለቀው ጠበል ብዙ የካንሰር (የነቀርሳ) በሽታ ታማሚዎች እየዳኑ ናቸው።
በዓለም አቀፍ ደረጃ መድኃኒት ታጥቶለት በዚህ ደዌ ለሚማቅቁት በሽተኞች የዚህ ቅዱስ ጻድቅ ጠበል በእምነት መጥተው ለሚጠመቁት ሁሉ ፍቱን መድኃኒት ስለሆነ ወጥተው በመጠመቅ ከበሽታቸው እንዲፈወሱ እግረ መንገዳችንን ሳንጠቁም አናልፍም።
ጻድቁ አባታችን አቡነ ዓብየ እግዚእ ከማረፋቸው በፊት አጋዕዝተ ዓለም ሥላሴ የተገለጹበት ቦታ ከምርፋቁ በላይ ባለው ተራራ ላይ ይገኛል።
ቅድስት ሥላሴ የገቡላቸው ቃል ኪዳንም -- በስምህ የዘከረ፣ የመጸወተ፣ ገድልህን የሰማ፣ ቤተ ክርስቲያንህን ያሳነጸ፣ በዚህ ቦታ መጥቶ የጸለየውንና የቆረበውን እስከ 30 ትውልድ እምርልሃለሁ ብሏቸዋል። የተሰቀልኩባት፣ የተቀበርኩባት የቀራንዮ፣ የእናቴ የማርያም እንዲሁም የቅዱሳኑን መቃብር አፈር በዚህ ቦታ ስለበተንከው ቦታው እንደ ኢየሩሳሌም ይሁንልህ ብሎአቸዋል።
ጻድቁ አቡነ ዓብየ እግዚእ በጾምና በጸሎት፣ በትምህርት እንዲሁም የክርስቶስን ወንጌል በማስፋፋት፣ አብያተ ክርስቲያናትን በማሳነጽ ሃይማኖታዊ ገድላቸውንና ሩጫቸውን ከፈጸሙ በኋላ በ 190 ዓመት ዕድሜያቸው ከዚህ ዓለም ወደ ማያልፈው ዓለም መንግሥተ ሰማያት ተሸጋግረዋል።
የጻድቁ መቃብር ያለው በቤተ ክርስቲያኑ መቅደስ ውስጥ ነው። ግንቦት 19 ቀን በገዳሙና በስማቸው በታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በታላቅ መንፈሳዊ አከባበር ይከበራል።
    የጻድቁ በረከት በጸሎትና ረድኤት ካንዣበበው መከራ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይጠብቅልን አሜን !!!