Saturday, December 22, 2012

ሐዋሪያዊው ቅዱስ እንድሪያስ ሰማእትነት


በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
 ታኅሣሥ ፬ ወበዛቲ ዕለት አዕረፈ ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ (በዚህ ዕለት የተመሰገነ ቅዱስ እንድርያስ በሰማዕትነት አረፈ።)
  “አማልክቲሆሙ ለአሕዛብ ዘወርቅ ወዘብሩር ግብረ እደ እጓለ እመሕያው”
 ቁጥሩ ከ12ቱ ሐዋርያት ነው:: የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስ ወንድም ነው::
እንድርያስ ማለት ጽኑዕ በኩር ማለት ነው። የቅዱስ ጴጥሮስ ወንድም ነው።
"በገሊላ ባሕር አጠገብ ሲመላለስም ሁለት ወንድማማች ጴጥሮስ የሚሉትን ስምዖንን ወንድሙንም እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፥ ዓሣ አጥማጆች ነበሩና። እርሱም፡- በኋላዬ ኑና ሰዎችን አጥማጆች እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ አላቸው። ወዲያውም መረባቸውን ትተው ተከተሉት።" ማቴ.፬፡፲፰ እንዲል እንዲል ወንጌል
ዓለምን ዞረው ለማስተማር ዕጣ ሲያወጡ ለሐዋርያው እንድርያስ ልዳ ደረሰው። ልዳ ማለት የቅዱስ ጊዮርጊስ አገር ናት። ከሰባ ሁለቱ አንዱ ፊሊሞናን አስከትሎ ሲሄድ ከቤተ ጣዖት ደረሰ። ፊሊሞና ድምጻዊ ነበር። ሊያስተምር ወደዚያች አገር ገባ፤ “አማልክቲሆሙ ለአሕዛብ ዘወርቅ ወዘብሩር ግብረ እደ እጓለ እመሕያው” እያለ ሲያስተምር አህዛብ ተሰበሰቡለት። አስተምሮ አሳምኗቸዋል። ልድያ የምትባል ሴትም ከሞተች በኋላ አስነስቷል። ከዚህ በኋላ ምዕማናንን ከገቢረ ጽድቅ ወደ ገቢረ ኃጢአት እንዳይመለሱ የሚመክሩ የሚያስተምሩ መምህራንን ካህናትን ሾሞላቸዋል።መካነ ጸሎት ሰጥቷቸው ወንጌል ካልደረሰበት ለማዳረስ እስከ ሀገረ በላዕተ ሰብእ ድረስ ሄዶ አስተምሯል። ጽኑዕ መባሉ ቅሉ ስለዚህ ነው። ከላይ በስዕሉ ላይ እንደምታዩት ያረፈው በመስቀል ተሰቅሎ ነው። ብዙዎች ትምህርቱን ሰምተው ተዓምሩን አይተው አምነው ተጠምቀዋል። ነቢያተ ሐሰት ካህናተ ጣኦት ጥቅም የሚቀርባቸው ሲሆን ኃያላኑን ሰብስበው ዋጋችሁን እንሰጣችኋለን ሐዋርያው እንድርያስን አጥፋልን አሉት ሲያስተምርም አገኙት፤ ለመግደል ሄደው በዚያው አምነውም ቀርተዋል። እነዚያም ካህናት ወይ ከገንዘባችን ወይ ከሕዝባችን አልሆን ብለው ሾተል ይዘው ወጡ፤ ሐዋርያው እንድርያስ ግን ከፍ ካለ ቦታ ላይ ቆሞ እንዲህ ሲል ሰበከ። "የአህዛብ ጣኦታት የሰው እጅ ስራ ናቸው ዓይን አላቸው አያዩም፤ ጆሮ አላቸው አይሰሙም፤ አፍንጫ አላቸው አያሸቱም፤ እጅ አላቸው አይዳስሱም፤ እግር አላቸው አይሄዱም በጉሮሮአቸውም አይናገሩም የሚሰሯቸው የሚያምኑባቸው ሁሉ እንደ እነርሱ ይሆናሉ፤ መዳን በእግዚአብሔር ነው እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው እያለ ሰበከ።” ከቃሉ ጣዕም ከአንደበቱን ቅልጥፍና ከነገሩ ማማር የተነሳ የወገባቸው ትጥቅ ተፈታ ሾተላቸውን ጣሉ፤ በጌታችን አምነው ተጠመቁ።
የሐዋርያው እና የሰማዕቱ የቅዱስ እንድርያስ ረድኤት በረከቱ ምልጃና ጸሎቱ ከሁላችን ጋር ለዘላለሙ ጸንቶ ይኑር።
ፀሐፊ ቤተማርያም
ዋቢ መጽሐፍት መዝገበ ታሪክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን አሜን።

No comments:

Post a Comment