Monday, November 19, 2012

ፃድቁ አባታችን አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ



      “እግዚአብሔር ያፈቅሮሙ ለጻድቃን እግዚአብሔር የዐቅቦሙ ለፈላስያን፡፡“ (እግዚአብሔር ጻድቃንን ይወድዳል፤ እግዚአብሔር ስደተኞችን ይጠብቃል፡፡)“ መዝ.፻፵፭፡፰ (145፡8)

                                        በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ
ዝክረ ጻድቅ ለዓለም ይሄሉ (የጸድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል።)†heart† መዝ.111፡6
ቅድመ ዓለም ዘሀሎ አለም ከመፈጠሩ በፊት ለነበረ ለእግዚአብሔር አብ እና የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋን ለለበሰ ለእግዚአብሔር ወልድ እንዲሁም ከእነሱ ባለመራቅ ለሚኖር ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም ምስጋና ይገባል፡፡ ስለ ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በማብዛት አይደለም በማሳነስ በማስረዘም አይደለም በማሳጠር እንድጽፍ ያነሳሳኝ እግዚአብሔር ክብርና ምስጋና ጌትነትና ውዳሴ ይገባዋል አሜን በእውነት፡፡

  “እግዚአብሔር ያፈቅሮሙ ለጻድቃን እግዚአብሔር የዐቅቦሙ ለፈላስያን፡፡“ (እግዚአብሔር ጻድቃንን ይወድዳል፤ እግዚአብሔር ስደተኞችን ይጠብቃል፡፡)“” መዝ.፻፵፭፡፰ (145፡8)
  አባታችን አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሀጋራቸው ንሂሳ ግብጽ ነው፡፡ አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ፡ ይባላሉ፡፡ ልጅ አጥተው 30 ዘመን ሲያዝኑ ኖረዋል፡፡ አንድ ቀን አቅሌሲያ ቤተ እግዚአብሔር ገብታ ከሥዕለ ሥላሴ ሥር ወድቃ ስትማጸን ክብሩ ከሰማይ ከፍታ የሚበጥ ልጅ እንኪ ተቀበይ የሚል ድምጽ ሰማች፡፡ በዚሁ መሰረት አባታችን መጋቢት 29 ተጸንሰው ታህሳስ 29 ተወለዱ፡፡ ዓይን በገለጹ ጊዜ ከሚታይ ነገር ላይ እንዲያርፍ እርሳቸውም በተወለዱ ጊዜ አፈፍ ተነስተው “ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ዘአውጻእከኒ እምጽ ልመት ውስተ ብረሃን” ብለው በማመስገናቸው ኋላም ምድራዊ መብል መጠጥ ሳይመገቡ ሳይጠጡ ለምስጋና ተግተው በመኖራቸው መላዕክትን ይመስላሉ፡፡
  ሦስት ዓመት ሲሆናቸው ቅዱስ ገብርኤል ከእመቤታችንና በገነት ካሉ ቅዱሳን ዘንድ አስባርኮ ገዳማውያን ካሉበት ምኔት ወስዶ ከበሩ አኖራቸው፡፡ አባ ዘመደ ብርሃን አሳድጎ አስተምሮ ከመዓርገ ምንኩስና አድርሷቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ “ሀብተ ፈውስ” ተሰቷቸዋል፡፡ በአንድ ቀን እልፍ እውራንንና አንካሳን ፈውሷል፡፡ ኋላ ግን ኤጲስ ቆጶሳቱ ካህናቱ ዝናቸውን ሰምተው እየመቱ ግብር የሚያስፈቷቸው ቢሆን ቅዱስ ገብርኤል በክንፉ ነጥቆ ከጌታ ፊት አቀረባቸው፡፡ በገድልህ በትሩፋትህ ከሞተ ነፍስ ከርደተ ገሃነም የሚድኑ ብዙ ነፍሳት አሉና ከሰው ተለይተህ ወደ ጫካ ግባ፡፡ ኑሮህም ከ60 አናብስተና ከ60 አናምርት ጋር ይሁን አላቸው፡፡ ጌታዬ ምን ተመግበው ይኖራሉ? ብለው ጌታን ጠየቁት፡፡ “ዘኬድከ ጸበለ-እገሪከ ይልህሱ ወበውእቱ ይጸግቡ…” የረገጥከውን ትቢያ ልሰው ያው ምግብ ሆኗቸው ይኖራሉ፡፡ ብሏቸው ውሳጤ ገዳም ገብተው ከአናብስትና አናምርት ጋር ይኖሩ ጀመር፡፡ ዳንኤል በአናብስት ጉድጓድ በጣለ ጊዜ አናብርቱ እንደ ድመት ከእግሩ በታች ሆነው እንደተገኙ የረገጡትን ትቢያ ይልሱ ይታዘዟቸውም ነበር፡፡ በዚህ መልኩ መልአኩ 30 ዓመት ከቆዩ በኋላ ጌታ ባንድነት በሦስትነት ተገልጾ “ምን ላድርግልህ ትሻለህ?” አላቸው፡፡ መጀመሪያ ላሉበት መጸለይ ይገባልና የምድረ ጋቦታን ሰዎች ማርልኝ አሉት፡፡ 3000 ሃጥአንን ከሲኦል አውጥቶ ገነት አግብቶላቸዋል፡፡ “ሑር ምድረ ኢትዮጵያ ወበህየኒ ሀላውከ ነፍሳት ዘታወጽኦሙ ወደ ኢትዮጵያ ሂድ” አላቸው፡፡ ቅዱስ ገብርኤል በሰረገላ ነፋስ ጭኖ ምድረ ከብድ አድርሷቸዋል፡፡ ዳግመኛም ወደ ዝቋላ ደብር ቅዱስ ወስዷቸው ከዚያ ሆነው በንጽሐ ልቦና የኢትዮጵያን ሕዝብ ሃጢአት አይተው ከባሕሩ በራሳቸው ቆመው ይጸልዩ ጀመር፡፡ አርባ ቀን ሲሆናቸው መልአኩ መጥቶ “ዘገብረ ተዝካረከ ወዘጸውዐ ስመከእምሕር ለከ ብሎሀል” አላቸው፡፡ መላ ኢትዮጵያን ካልማረልኝ አልወጣም ብለው መቶ አመት ሲጸልዩ ኑረዋል፡፡ ከመቶ አመት በዃላ ጌታ “ተንስእ ወጻእ መሐርኩ ለከ ኩሎ ኢትዮጵያ ምሬለሃለሁ ውጣ” ብሏቸው ወጥተዋል፡፡
  ከዚህ በኋላ ምድረ ከብድ ወርደው ከምድር በላይ ከሰማይ በታች ሆነው ሰባት ዓመት እንደ ትኩል አምድ ሆነው ዓይናቸውን ሳይከድኑ ሰባት ዓመት ቆመው ጸልየዋል፡፡ ሰይጣንም በምቀኝነት ተነሳስቶ ቁራን መስሎ መጥቶ አይናቸውን አንቁሮ አሳወራቸው፡፡ ሁለት ሱባኤ ሲፈጽሙ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል መጥተው እፍ ብሏቸው አድነዋቸዋል፡፡ ከዚያ ተነስተው ወደ ዝቋላ ሲሄዱ ሥላሴን በአምሳለ አረጋውያን ከጥላ ስር አርፈው አገኟቸው፡፡ በእግዚአብሔር ዙፋን ተማጽነናል አዝለህ አንድ አንድ ምዕራፍ ሸኘን አሏቸው፡፡ አዝለው ከሸኙአቸው በኋላ በአንድነት በሦስትነት ሆኖ ታያቸው ደንግጠው ወደቁ፡፡ አንስተው ዝቋላ ወርደህ ጠላቶችህን ተበቀላቸው አሏቸው፡፡በዘባነ መብረቅ ደርሰው ሰባቱን ሊቃነ መላእክት አጋዥ አርድገው እልፍ አዕላፍ አጋንንትን በማጭድ አጭደዋል፡፡ እንዲህ ለሰሚዕ እፁብ በሆነ ግብር ዓመት በኢትዮጵያ 262 ኖረው በ562 ዓመታቸው በተስፋቸው ያመነውን በኪዳናቸው የተማጸነ ጌታ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ሊምርላቸው ተስፋቸውን ተቀብለው  በዕለት በዕለተ እሁድ ዐርፈዋል፡፡
  መላእክት በአክናፈ እሳት ኢየሩሳሌም ወስደው በየማነ ምስዋዕ ቀብረዋቸዋል፡፡
ሮሜ 12፡12፣ 15፡30፣ያዕ5፡16፣ መዝ.88፡3፣111፡6 ምሳ.10፡7 ማቴ10፡40-42
  ወደ ኢትዮጵያ የመጡት በቅዱስ ላሊበላ ዘመነ መንግስት መሆኑ ስለሚታወቅ ከ9- 14ኛው ም/ዓ ድ/ል/ክ መሆኑ ነው፡፡
  ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣኝ፣ ካለማወቅ ወደ መረዳት ያደረሰኝ አነሳስቶ ላስጀመረኝ አስጀምሮ ላስፈጸመኝ ጥንት ላሌለው ቀዳማዊ ፍጻሜ ላሌለው ድህራዊ ያልኖረበት ጊዜ የሌለ የማይኖርበት ጊዜም የማይኖር የዘላለም ንጉስ ሁሉን ቻይ ፈጣሪ እግዚአብሔርን በራስ ፀጉሬ ቁትር በአጥንቶቼም ልክ አመሰግናለሁ፡፡
  በሰማይ ያሉ መላእክት በምድርም የሚኖሩ የአዳም ዘር ሁሉ የሚያመሰግኗት በአማላጅነቷ ሁል ጊዜ የማትለየኝ ከፀሐይ ሰባት እጅ የምታበራ የብርሃን እናት የሁሉ እመቤት የአምላክ እናት ከተመረጡ የተመረጠች ከተለዩ የተለየች ከተከበሩ የተከበረች እናቴ እመቤቴ ድንግል ማርያም በቃላት ልገልጸው ከምችለው በላይ አመሰግናለሁ፡፡
ምንጭ፡- መዝገበ ታሪክ፣ ነገረ ቅዱሳን፣ የወርሃ ጥቅምት ስንክ ሳርና ገድላቸው፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘበቅዱሳኒሁ ይሴባሕ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ወለዓለም ዓለም አሜን፡፡ ወአሜን ለይኩን ለይኩን፡፡

No comments:

Post a Comment