Thursday, December 13, 2012

አባ አጋቶን እና አባ መቃርዮስን

አባ መቃሪዮስ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::

 “በኢሩቤል ላይ የምትኖር  የቀለያትንም (ጥልቅ ባሕርንም) ጥልቀት የምትመለከት ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ አቤቱ ስለቅዱሳን ሁሉ ብለህ ማረን ይቅርም በለን ደግ ሰው አልቆአልና አሜን።” ይህ የቅዱሳን ሁሉ ልመና ነው።
በመስከረም  14 የሚዘከሩ ቅዱሳን አባቶች
የአባ አጋቶን እና የአባ መቃርዮስን መታሰቢያ በዓላቸዉን ትዘክራለች።
    “ቅዱሳን በመለኮታዊ ማዕጠንት የተቀጣጠሉ ዕጣን ሲሆኑ የተቀጣጠሉበትም በፈጣሪያቸው ፍቅር ነው።” (ብጹህ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ)
    “የቅዱሳን ሕይወት ተርታ ታሪክ ወይም ተረት አይደለም፤ ይልቁንስ እግዚአብሔርን የሚከተሉና በሥራቸው ሁሉ የእርሱ ጥበቃ ያልተለያቸው ሰዎች ታሪክ ነው።” (ብጹህ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ)
    ቅዱስ ማለት በግእዝ ጽሩይ፣ ንጹሕ፣ ንዑድ፣ ክቡር፣ ልዩ መሆን ማለት ነው።
    ይህ ቃል ለእግዚአብሔር የባሕርዩ መገለጫ ነው፤ እግዚአብሔር በባሕርይው ቅዱስ ነውና። በባሕርዩ ቅዱስ የሆነውን አምላክ የሚያገለግሉ 
መላእክትንና ደጋግ ሰዎች የስሙ ቀዳሾች የክብሩ ወራሾች ናቸውና ቅዱሳን ይባላሉ። ቅዱሳን አካሄዳቸው ከእግዚአብሔር ጋር ያደረጉ፤ ሕጉን የጠበቁ ያስጠበቁ፣በሕጉ ከታዘዘውም በላይ በገድል በትሩፋት ጸንተው የኖሩ ናቸው። ስለ ቅዱስ ሥራቸው እግዚአብሔር በቅድስና ያከበራቸው ናቸው። ልዑል እግዚአብሔር በአራያው ፈጠረን ሲባል ቅሉ እርሱ ቅዱስ ተብሎ እኛን ቅዱሳን እርሱ ጻድቅ ተብሎ እኛን ጻድቃን እንዳሰኘን ማለታችን መሆኑ እርግጥ ነው። ስለ ቅዱሳን መናገር መመስከር ደግሞ ስለ ቀደሳቸው እግዚአብሔር መመስከር መናገር ነው።
    መቼም ያልተማረ ካልሆነ በስተቀር ቅዱሳን ፍጡራን መሆናቸውን የማያውቅ ማንም የለም፤ ከፍጡራን የሚለያቸው ግን በሃይማኖታቸው በበጎ ምግባራቸው በእግዚአብሔር ፊት ያገኙት ሞገስ ነው።
    ቅዱሳን ስንል እንደየቅድስናቸው ቅዱሳን ነብያት፣ ቅዱሳን ሐዋርያት፣ ቅዱሳን ጻድቃን፣ ቅዱሳን ሰማዕታት፣ ቅዱሳን አበው፣ ቅዱሳን ነገስታት፣ ቅዱሳን ሊቃውንት፣ ቅዱሳን ጳጳሳት፣ ቅዱሳን መነኮሳት (ደናግል)፣ ቅዱሳት አንስት፣ ቅዱሳን መላእክት፣ መካናት፣ መጽሐፍት፣ ናቸው። ከነዚህ ደግሞ በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን በዛሬዋ ዕለት መታሰቢያቸው ከሚዘከርላቸው ቅዱሳን መነኮሳት (ደናግል) ውስጥ አባ አጋቶንና አባ መቃርዮስ ባጭሩ እንመልከት።

   አባ አጋቶንን ያስተማረዉና ያሳደገዉ አባ ጴሜን ነዉ፡፡ በመቀጠልም ከአባ እስክንድር ጋር በአስቄጥስ ገዳም ኖሯል፡፡ አንድ ጊዜ አንድ አባት ወደ ኣባ አጋቶን ገዳም ሄዶ …… ”ከወንድሞች ጋር መኖር እሻ ነበር እስቲ ምከረኝ አለዉ”…….አባ አጋቶንም “በኑሮህ ሁሉ የእንግዳ ሰዉ ዓይነት ልቡና ይኑርህ፣ ልክ በመጀመሪያ ያገኘሃቸዉ ቀን የምትሆነዉን ዓይነት፤ በጣምም አትቅረባቸዉ በጣምም አትራቃቸዉ…..”አለዉ፡፡ በዚህ ጊዜ አባ መቃርዮስ “ይህ መቀራረብ ምን ያስከትላል?” ሲል ጠየቀዉ፡፡ አባ አጋቶንም

    “ያማ እንደ ኃይለኛ ዐዉሎ ነፋስ ያለ ነዉ ሊንሳፈፍ የሚችለዉን ሁሉ እያነሳ የዛፎችን ፍሬ ያበላሸዋል፡፡” አባ መቃርዮስም “ያለ መጠን መናገር ይህን ያህል ይጎዳል። “እንዴት ሲል ጠየቀዉ”….አባ አጋቶንም “የማይቆጣጠሩትን ምላስ ያህል መጥፎ ጾር የለም ፣እርሷ የፈተናዎች ሁሉ እናት ናት፡፡” አለዉ…. “ጠንካራ መነኩሴ ማለት ተዋጊ ነዉ ብሎ መክሮአቸዋል፡፡”

   አባ መቃርዮስ ታላቁ የተወለደዉ በ፫፻ ዓ.ም በንስጥራ አካባቢ ነዉ፡፡ በገዳመ አስቄጥስ የምንኩስና ሕይወትን ካደራጁ አበዉ አንዱ ነዉ፡፡ ከአባ እንጦንስ አባ ጳውሊ ጋር በ፫ኛ ደረጃ ላይ ያለ ታላቅ አበ መነኮሳት ከሆኑት አንዱ እሳቸው ናቸው።
    ታድያ ቅዱሳን መነኮሳት መላ ዘመናቸውን ከጣዕመ ዓለምና ከተድላ ዓለም ተለይቶ ቤት ልስራ፣ ዘር ልዝራ፣ ሳይሉ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ በምናኔ በየዋሻው በየገደሉ፣ በየገዳማቱ ጸንተው የኖሩ ናቸው። ለዚህም ነው ቅዱ ጳውሎስ “ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ።” በማለት ዕብ.፲፩፡፴፰ ላይ የተናገረው።
የሰው ልጆች ፪ (ሁለት) አማራጮች ብቻ አላቸው። ወይ አግብተው በጋብቻ ሕግ መኖር፤ አለያ መንኩሶ በምንኩስና ሕይወት ይኖራል። ከዚህ የተለየ ሕይወት የለም።
    “ሰው ሁሉ እንደ እኔ ሊሆን እወዳለሁና፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው።” ፩ቆሮ.፯፡፯
    ”ከሴት ጋር አለመገናኘት ለሰው መልካም ነው። ነገር ግን ስለ ዝሙት ጠንቅ ለእያንዳንዱ ለራሱ ሚስት ትኑረው ለእያንዳንዲቱ ደግሞ ለራስዋ ባል ይኑራት።” (፩ቆሮ.፯፡፩-፪)
     “እንደ እኔ ቢኖሩ ለእነርሱ መልካም ነው፤ ነገር ግን በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ።” (፩ቆሮ.፯፡፰-፱) ብርሃነ ዓለም ቅ/ጳውሎስ ይህን ሁሉ ሲናገር የጋብቻን ቅድስናንም ሳይናገር አላለፈም “መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል።” ዕብ.፲፫፡፬
እሱ ባስጓዘን መንገድ እንድንጓዝ መድኃኔአለም ይርዳን አሜን።
የቅዱሳን ሁሉ በረከትና ርድኤታቸው አይለየን አሜን።

       ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣኝ፣ ካለማወቅ ወደ መረዳት ያደረሰኝ አነሳስቶ ላስጀመረኝ አስጀምሮ ላስፈጸመኝ ጥንት ላሌለው ቀዳማዊ ፍጻሜ ላሌለው ድህራዊ ያልኖረበት ጊዜ የሌለ የማይኖርበት ጊዜም የማይኖር የዘላለም ንጉስ ሁሉን ቻይ ፈጣሪ እግዚአብሔርን በራስ ፀጉሬ ቁትር በአጥንቶቼም ልክ አመሰግናለሁ፡፡ እድሜ ለንሰሐ ዘመን ለፍሰሃ ሰጥቶኝ ይህችን ታህል ስለ አባታችን እንድመሰክር የረደኝ አምላክ ስሙ የተመሰገነ ይሁን።
    አመስግኛት የማልሰለች፣ ስለሷ ተናግሬ የማይደክመኝ፣ በሰማይ ያሉ መላእክት በምድርም የሚኖሩ የአዳም ዘር ሁሉ የሚያመሰግኗት በአማላጅነቷ ሁል ጊዜ የማትለየኝ ከፀሐይ ሰባት እጅ የምታበራ የብርሃን እናት የሁሉ እመቤት የአምላክ እናት ከተመረጡ የተመረጠች ከተለዩ የተለየች ከተከበሩ የተከበረች እናቴ እመቤቴ ድንግል ማርያም በቃላት ልገልጸው ከምችለው በላይ አመሰግናለሁ፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘበቅዱሳኒሁ ይሴባሕ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ወለዓለም ዓለም አሜን፡፡ ወአሜን ለይኩን ለይኩን፡፡

No comments:

Post a Comment