Wednesday, December 26, 2012

አቡነ ተክለሀይማኖት

            በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
   እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በፍርኩታ በምድር ጕድጓድም ተቅበዘበዙ። ዕብ.11፡33-40
ስለ አምላካቸውም ሲሉ ሁሉን ትተው፣ ሁሉን ንቀው አምላካቸውን እንደተከተሉ መጽሐፍ ቅዱሳችን ያስረዳል።
ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ ስለ እኔ ግን ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል። ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል? የሰው ልጅ ከመላእክቱ ጋር በአባቱ ክብር ይመጣ ዘንድ አለውና፤ ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው ያስረክበዋል።(ማቴ.16፡25-27
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም ስለቅዱሳኑ ሲናገር፤ “እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው።” ይላል። መዝ. 67/68፡35
ስለ ጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ፣ እንዲሁም የሚሰደዱ ብጹዓን ናቸው ይጠግባሉና፣ መጽናናትንም ያገኛሉና…+++ ጌታ በተራራ ስብከቱ ከተናገራቸው፣ ካስተማራቸው የሕይወት ምግብ የሆነ ቃሉ በማቴ.5፡1-ፍጻሜ
እግዚአብሔር አምላካችን ሰማዕታትን በደም፤ ቅዱሳንን በገዳም፤ ሐዋርያትን በአጽናፈ ዓለም፤ መላእክትን በአጽራርያም እንዳጸናቸው እኛ ሁላችንንም በኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነታችን በቅድስት ቤተክርስቲያን በበጎ ምግባር በጾም በጸሎትና በትሩፋት ያጽናን ስለ አባታችን ተክለሀይማኖት ታሪክ ትንሽ ልበል

      አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቡልጋ ደብረ ጽላልሽ ወይም ዞረሬ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሰበካ ክልል ከአባታቸው ከካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ቅድስት እግዚእ ኃረያ መጋቢት ፳፬ ቀን ተፀንሰው፤ በ፲፩፻፺፯ ዓ.ም ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ተወለዱ፡፡ በተወለዱ በሦስት ቀናቸው ከእናታቸው እቅፍ ወርደው «አሐዱ አብ ቅዱስ፣አሐዱ ወልድ ቅዱስ፣ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ» ብለው ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸውም ፍስሐ ጽዮን አሏቸው፡፡ ትርጓሜውም የጽዮን ተድላዋ ደስታዋ ማለት ነው፡፡

በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በአሥራ አምስት ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ /ጌርሎስ/ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡ በዚህም ቅድስት ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡

ከዕለታት በአንዱ ቀን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከጓደኞቻቸው ጋር ወደ ዱር አደን ሄደው ሳለ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ ለኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ሐዲስ ሐዋርያ አድርጎ መረጣቸው። ስማቸውንም «ተክለ ኃሃይማኖት» አለው፡፡ ትርጓሜውም የኃይማኖት ፍሬ ማለት ነው፡፡

አባታችንም ሐዋርያዊ ጉዟቸውን ሲጀምሩ «አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ . . . ደካማ ለሆንኩ ለእኔ ያለ አንተ የሚያፀናኝ የለም። ለምፍገመገም ለእኔ ያለ አንተ ደጋፊ የለኝም። ለወደቅሁ ለእኔ ያለአንተ የሚያነሳኝ የለም። ለአዘንኩ ለእኔ ያለአንተ የሚያረጋጋኝ የለም። ለድሀው ለእኔ ያለ አንተ መጠጊያ የለኝም፡፡» /ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ ፳፰ ቁ ፪ - ፫/
ይህን ብለው ትሕትና በተሞላበትና በተሰበረ ልብ ወደ ፈጣሪያቸው ከለመኑ በኋላ በልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍለ ሀገራት ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ሃይማኖት መልሰዋል፡፡ በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ፀሐይ ተብለዋል፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን ክታቡ ስለ ቅዱሳን መንፈሳዊ ተጋድሎ ሲገልፅ:-
«እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሱ» /ዕብ. ምዕ ፲፩ ቁ ፴፫ / እንዳለ አባታችን ቅዱስ ተክለ ሃይማኖትም በመንፈሳዊ ተጋድሎ እንዲሁም በትህትና በተአምራት አላዊ የነበረውን ንጉሥ ሞቶሎሚን ወደ ክርስትና መልሰዋል፡፡
«ጽድቅን አደረጉ» እንዳለው አባታችን ወንጌልን በተጋድሎ ሕይወታቸው ተርጉመዋል፡፡
«የአንበሶችን አፍ ዘጉ» ምዕ ፲፩ ቁ ፴፫ /ምዕ ፲፩ ቁ ፴፬ /እንዳለው አባታችንም የአውሬውን ፥ የዘንዶውን ራስ ቀጥቅጠዋል።
«ከሰይፍ ስለት አመለጡ» እንዳለው አባታችንም ሞቶሎሚ ከወረወረው ጦር በተአምራት ድነዋል፡፡
«ከድካማቸው በረቱ» እንዳለው አባታችንም ያለ ዕረፍት በብዙ ተጋድሎ በጾምና በስግደት በብዙ መከራ በርትተዋል፡፡
ይህን ሁሉ ገድልና ትሩፋት እየፈጸሙ ዕረፍታቸውም በደረሰ ጊዜ ደቀመዝሙሮቻቸውን «ልጆቼ ሆይ ሁሉም መነኮስ መንግሥተ ሰማይ ይገባል ማለት አይደለም፤ ዓለምን በሚገባ የናቀ ብቻ ይገባል እንጂ መጀመሪያ የእግዚአብሔርን ጽድቁን ብቻ ፈልጉ፤ ጾምና ጸሎትን አዘውትሩ፤ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ፤ ትእዛዛቱንም አጥብቃችሁ ጠብቁ እያሉ ይመክሯቸው ነበር. . .» በኋላም «ለዓለም ጨው ለራሴ አልጫ ሆንኩ፤ ለዓለም ብርሃን ለራሴ ጨለማ ሆንኩ፣ ከእውነተኛው ዳኛ ከጌታዬ ፊት ስቆም ምን እመልሳለሁ?» እያሉ በፍጹም ትህትና እና በልዩ መንፈሳዊ ተመስጦ ይጸልዩ ነበር፡፡

በመጨረሻም አባታችን በነሐሴ ፳፬ ቀን ዕረፍታቸው ሆነ። በዚህም መሠረት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ለእኚህ ዕረፍታቸው በእግዚአብሔር ፊት ለከበረና ብዙ ክብር ለተሰጣቸው ለጻድቁ ተክለ ሃይማኖት በየዓመቱ በነሐሴ ፳፬ ቀን በዓለ ዕረፍታቸውን በታላቅ ድምቀት ታከብራለች፡፡ እኛንም ከጻድቁ ረድኤት በረከት ይክፈለን፡፡
ሰላም ለዝክረ ስምከ በጥንተ ፊደሉ መስቀል ስም ክቡር ወስም ልዑል።
ተክለሃማኖት ማቴዎስ በዓለ ቀዳማይ ወንጌል
ከመ እወድሰከ መጠነ አውሥኦተ እክል።
ማዕሠረ ልሳንየ ትፍታሕ ማርያም ድንግል።

ትርጉም ‹‹ የስምህ መነሻ ፊደል የመስቀል ምልክት ለሆነው እና ክቡር ገናና ለሆነው ስም አጠራርህ ሰላም እላለው ። የወንጌል ተቀዳሚ ስም ማቴዎስ የተባልክ ተክለሃይማኖት ሆይ እንደ ችሎታዬ አመሰግንህ ዘንድ አንደበቴ ትፈታልኝ ዘንድ ድንግል ማርያምን እማልዳለሁ።››

የአባታችን የአቡነ ተክለሃይማኖትን ታሪክ በዘመን እየከፈልን ባጭሩ ስንመለከተው ደግሞ፡-
የአባታችን የአቡነ ተክለሃይማኖት አባት ቅዱስ ፀጋዘአብ በሸዋ ቡልጋ ደብረ ጽላልሽ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አገልጋይ ካህን ነበሩ፡፡ መጋቢት 24 ቀን አባታችን ተክለሃይማኖት ተፀነሱ በታህሣስ 24 ቀን በ1190 ዓ.ም አባታችን ጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት ከእናታቸው ከቅድስት እግዚሐሪያ እና ከአባታቸው ከቅዱስ ፀጋዘአብ ተወለዱ፡፡ በተወለዱ በ3ኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ፣ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፣ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ ብለው ፈጣሪያቸውን አመሠገኑ፡፡ በተወለዱ በ40ኛው ቀን ክርስትናን በመነሳት ፍስሐ ጽዮን “የጽዮን ደስታ” ተበለው ተጠሩ፡፡ አባታችን 7 ዓመት እስከሞላቸው ድረስ ከአባታቸው ከፀጋዘአብ ዘንድ እየተማሩ አደጉ፡፡ አባታችን በ15 ዓመታቸው ዲቁናን ከጌርሎስ ዘንድ ተቀበሉ፡፡ አባታችን በ22 ዓመታቸው ከአቡነ ጌርሎስ ዘንድ ቅስናን ተቀበሉ፡፡ በከተታ አውራጃ 3 ዓመት ወንጌልን እያስተማሩ ብዙ ድንቅ ነገርን አደረጉ፡፡ አባታችን በዳዊት ፀሎት ከነቢያት ምስጋና ሌሊቱን ሙሉ ይተጉ ነበር በያንዳንዱ መዝሙርም 10፣ 10 ስግደትን ይሰግዱ ነበር፡፡ በሕዳር 24 ቀን ቅዱስ ሚካኤል ወደ ላይ ነጠቃቸው (አወጣቸው) ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር 25ኛ ካህን ሆነው የሥላሴን መንበረን “አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ” በማለት አጥነዋል፡፡ በሐይቅ 10 ዓመት በደብረዳሞ 12 ዓመት ኖረዋል፡፡ አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖት በ1267 ዓ.ም ደብረ ሊባኖስን በአት አድርገው ኖሩ፡፡ ለ22 ዓመት ቆመው በመፀለይ የአንድ እግራቸው አገዳ ተሠበረ ደቀ መዝሙሮቻቸው በጨርቅ ጠቅልለው ቀበሩት፡፡ በአንድ እግራቸው ለ7 ዓመት በፀሎት ቆሙ በጠቅላላው ለ29 ዓመት በፀሎት ከቆሙ በኋላ በ99 ዓመት ከ10 ወር ከ10 ቀን ነሐሴ 24 ቀን 1290 ዓ.ም አረፉ አባታችን ባረፉ 54 ዓመታቸው በ1354 ዓ.ም ለአባታችን ለአቡነ እዝቅያስ ተገልጸው አጽማቸው ከደብረ አስቦ ወደ ደብረ ሊባኖስ ግንቦት 12 ቀን እንዲፈልስ አድርገዋል፡፡

ህዳር 24 ቀን 25ተኛ ካህናተ ሰማይ ሆነው በሠማይ የሥላሴን መንበር ያጠኑበት
ታህሳስ 24 ቀን የአባታችን ልደት
ጥር 24 ቀን የአባታችን ስባረ አጽም
መጋቢት 24 ቀን የአባታችን ጽንሠት
ግንቦት 12 ቀን የአባታችን ፍልሰተ አጽም
ነሐሴ 24 ቀን የአባታችን እረፍት
የአባታችን ቡራኬ ይድረሰን አሜን!
“ልጆቼ ሆይ ሁሉም መነኩሴ መንግሥተ ሰማይ ይገባል ማለት አይደለም ዓለምን በሚገባ የናቀ ብቻ ይገባል እንጂ መጀመሪያ የእግዚአብሔርን ጽድቁን ብቻ ፈልጉ ጾምና ጸሎትን አዘውትሩ እርስ በእርሳችሁም ተዋደዱ ትዕዛዛቱንም ጠብቁ” የሐዲስ ኪዳኑ ሙሴ የአባታችን የተክለሃይማኖት ምክር

በደብረ አሚን ከሚገኘው ገድላቸው ደግሞ ባጭሩ፡-

የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው መ ምሳሌ 10፡ 7

የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው እንዳሉ ነቢያት እኛም ነብያትን ሐዋርያትን ጻድቃንን ሰማእታትን አክብረን ብንቀበላቸው በረከተ ስጋ በረከተ ነፍስ የምናገኝበት መሆኑንን በማሰብ ከጻድቃን መካከል አንዱ የሆኑትን የቅዱስ ተክለሃይማኖት ተጋድ
ሎ በትንሹ እንመልከት::አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖት ቡልጋ ደብረ ጽላሎሽ ወይም ዞረሬ ቅዱድ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ክልል ከአባታቸው ከጸጋዘአብ ከእናታቸው ከእግዟእኅረያ ታኅሣሥ 24 ተወለዱ ::በወላጅ አባታቸው በካህኑ ጸጋዘአብ ግብረ ዲቁናን ስርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው ቄርሎስ ከተባሉት ግብጻዊ ጳጳስ በ15 አመታቸው ዲቁናን ተቀበሉ::እንዲሁም እድሜያቸው 22 አመት ሲሆን ከላይ ስማቸው ከተገለጹት ጳጳስ የቅስናን ማዕረግ ተቀበሉ ከዚህ በኋላ ለህዝቡ ወንጌል እየሰበኩ ጣዖት አጋንንትን እያደቀቁ ህዝቡን አምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር መልሰው አባኢየሱስ ሞዓ ወደ ሚገኙበት ገዳም ሐይቅ እስጢፋኖስ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ሃይቁን በእግራቸው እንደ ደረቅ መሬት በመርገጥ ወደ ደሴቱ በመግባት የምንኩስናን በመቀጠል ከአባ ኢየሱስ ሞዓ እጅም የምንኩስናን ቀሚስ የንጽህናን ምልክት ተቀብለው ለ12 ዓመታት አቡነ አረጋዊ ወዳቀኑበት ገዳም ደብረ ዳሞ በመግባት በጊዜው ከነበሩት አበምኔት ከአባ ዮሐኒ ቆብና አስኬማ ተቀብለው በገድል በቱሩፋት መንፈሳዊ ተጋድሎዋቸውን ቀጠሉ::ከዚህ ሁሉ በኋላ በደብረ ሊባኖስ ካለችው ገዳመ አስቦ ዋሻ በመግባት ስምንት ጦሮችን ሁለቱን በፊት ሁለቱን በኋላ ሁለቱን በቀኝ ሁለቱን በግራ አስተክለው እጆቻቸውን በትምህርተ መስቀል አምሳል በመዘርጋት የክርስቶስን ህማምና ሞት ነገረ መስቀሉን በማሰብ በተመስጦ ሌትና ቀን ያለ ማቋረጥ በጾም በጸሎት በአርምሞ ተወስነው ሲጋደሉ ከቁመት ብዛት የተነሳ ጥር 24 ቀን የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች እግራቸው እስኪሰበር በጸሎት የቆዩባቸው አመታት 22 ናቸው ::በመአልትና በሌሊት በትጋትና በቁመት በተጋድሎ ብዛት አንዲት የእግራቸው አገዳ ስትሰበር ዕድሜያቸው 92 አመት ሆኖ ነበር::ከዚህ በኋላ ለ7 አመታት በአንድ እግራቸው ብቻ በመቆም ያለ ምግብ ሌትም ቀን ምእንቅልፍ በአይናቸው ሳይዞር እንደ ምሰሶ ጸንተው በተመስጦ በትጋት ለሰው ዘር ሁሉ ድኅነት ሲለምኑ ኖረዋል ::በመጨረሻም አባታችን በነሐሴ ፳፬ ቀን ዕረፍታቸው ሆነ::
የአባታችን የአቡነ ተክለ ሀይማኖት ምልጃና ጸሎታቸው ረድዔትና በረከታቸው በኛ በልጆቻቸው ላይ ይደርብን አሜን!

 ምንጭ ታምረ ተክለሐይማኖት ዘደብረ አሚን

 የእግዚአብሔር፣ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን መላእክት ተራዳኢነት፣ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት፣ የቅዱሳን አበው መነኮሳት፣ የቅዱሳት አንስት፣ የደናግላንና የቅዱሳን ሁሉ ምልጃና ቃል-ኪዳናቸው ባለንበት ከሁላችን ጋር
  ወስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘበቅዱሳኒሁ ይሴባሕ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ወለዓለም ዓለም አሜን፡፡ ወአሜን ለይኩን ለይኩን፡፡

No comments:

Post a Comment