Tuesday, December 4, 2012

ሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ


                          ሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ
                     በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን
        ከቅዱሳን ሰማዕታት አንዱ የሆነው ማር ሚና በ 4ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ተጋድሎውን የፈፀመ ግብፃዊ ሰማዕት ሲሆን ህዳር 15 ቀን የሚነበበው ስንክሳር ቅዱስ ሚናስ በሚል ስያሜ ይገልፀዋል። በሶሪያ ቋንቋ ማር የሚለው ቃል ‘ቅዱስ’ የሚል ትርጉም ሲኖረው ለወንድ የሚሰጥ ቅጥያ ሲሆን ለሴት ደግሞ ማርታ ይሆናል ይሄውም ቅድስት ማለት ነው።
ቅዱስ ሚናስ ከእናቱ ከአውፌምያ እና ከአባቱ ከአውዶስዮስ ልዩ ስሙ ኒቆስ ሻቲ በተባለ መንደር በ 276 ዓ∙ም ተወለደ። እናቱ አውፌምያ ልጅ መውለድ ባለመቻሏ ታዝንና ትጨነቅ ነበር። ወደ ቤተ-ክርስቲያን ስትሄድም እናቶች ልጆቻቸውን ሲያቆርቡ ስታይ በማልቀስ ፈጣሪዋን ልጅ እንዲሰ
ጣት ትለምን ነበር። እግዚአብሔርም የልመናዋን ቃል ሰምቶ ወንድ ልጅ ሰጣት።
አባቱ አውዶስዮስ የናይል ዴልታ አስተዳዳሪ የነበረ ሲሆን ለህዝቡ ባለው ፍቅርና ሐዘኔታ እንዲሁም በትክክለኛ ፍርድ ሰጭነቱ በአካባቢው ሰው ተወዳጅነትን ያተረፈ ሰው ነበር። አውፌምያም እግዚአብሔርን የምትፈራና ባለቤቷ በሚፈፅማቸው ቀና ምግባሮች ሁሉ ከጎኑ ሆና የምትደግፈውና የምታበረታታው ሴት ነበረች።
ቅዱስ ሚናስ ወላጆቹን ያጣው በልጅነት ጊዜው ሲሆን ከወላጆቹ የወረሰውንም ሃብትና ንብረት በመሸጥና ለድሆች በማከፋፈል እርሱ ግን ይህችን አለም ንቆ መነነ። በዘመኑ በነበሩ ጣዖት አምላኪ ነገስታት ተይዞ ለጣዖት አልሰግድም በማለቱ አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ ይህም የሆነው በ 24 ዓመቱ ነው።
ማር ሚና (ቅዱስ ሚናስ) በኢትዮጵያ ብዙም ባይታወቅም በጣና ቂርቆስ ከሰማዕቱ ከቅዱስ ቂርቆስና ከቅዱስ እስጢፋኖስ ጋር መቅደስ ታንፆለት እንደነበር
"ጠቢበ ጠቢባን ቂርቆስ ወእማዕምራን ማዕምር
ሐውፃ ለመቅደስከ እንተ ተሃንፀት በባህር፡
ምስለ እስጢፋኖስ ሰማዕት ወሚናስ ፍቁር።" የሚለው የመልክዐ ቂርቆስ ንባብ ምስክር ነው። የጠቢባን ጠቢብ የአዋቂዎች አዋቂ የምትሆን ቂርቆስ ሆይ ከሰማዕቱ እስጢፋኖስና ከተወዳጁ ከሚናስ ጋር በባህር ላይ የታነፀች መቅደስህን ጎብኛት ማለት ነው። እዚሁ መልክዕ ውስጥ በግብፅ በታወቀው የስም አጠራሩ "ሚና" በማለት የሚጠራውን ንባብ እናገኛለን።
"ሰላም ዕብል ዘምስለ ካልዕከ ሚና ፤
ቂርቆስ ሕፃን ዘእያብፅሕኮ ውርዝውና" ለጉልምስና ያልበቃህ ሕፃን ቂርቆስ ሆይ ከጓደኛህ ከሚና ጋር ሰላም እልሃለሁ (ሰላምታ ላንተ ይሁን) ማለት ነው።በማለት በካይሮ አባስያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን ቅድስት ማርያም ሰ/ት/ቤት የተዘጋጀው የሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ እና የፓትርያሪክ ቄርሎስ ፮ኛ የህይወት ታሪክ በሚል የተዘጋጀው መፅሃፍ ይገልጻል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ስለሚገኘው ብቸኛው የቅዱስ ሚናስ ቤተ-ክርሰቲያን ምን ያህል ያውቃሉ?
የቅዱስ ሚናስ ቤተ-ክርሰቲያን ከባህር ዳር ከተማ በግምት 23 ኪ∙ሜ ርቀት ላይ በምዕራብ ጎጃም እና በደቡብ ጎንደር መሀከል ወይም በደራ ክፍለሃገር ከአቡነ ሐራ ድንግል ገዳም በግምት ከ3-4 ኪ∙ሜ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን አካባቢውም በተለምዶ ሚናስ እየተባለ ይጠራል።
ቤተ-ክርስቲያኑ የተተከለበት ዘመን በውል ባይታወቅም ቤተክርስቲያኑ ግን በአፄ ፋስል ዘመነ መንግስት እንደነበር ገድለ አቡነ ሐራ ድንግል ያስረዳል።
በአፄ ሱስንዮስ ዘመነ መንግስት በ 1597 ዓ∙ም በነበረው የሐይማኖት መፋለስ ቅዱሳን በሃይማኖታቸው ሲሰደዱ ብዙ እንግልት መከራ እና ስቃይ ሲደርስባቸው በነበረበት በዚያ ዘመን የንጉሱ ግብረ አበሮች እና አድርባዮች ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን ሲመዘበሩና በእሳት ሲያቃጥሉ ይህን ቤተ-ክርስቲያን ግን ለማቃጠል ቢሞክሩም በእግዚአብሔር ተዓምር የቤተክርስቲያኑን በር መክፈትም ሆነ ቤተ-ክርስቲያኑን ማቃጠል አልተቻላቸውም ነበር። ከዚያን ጊዜ በኋላም ለማንም ሊከፈት ባለመቻሉ ለ 17 ዓመት ተዘግቶ እንደቆየ አባቶች ይናገራሉ።
ገድለ አቡነ ሐራ ድንግልም የሃይማኖት መፍለስም ከሆነ ከ 16 ዓመት በኋላ በአፄ ፋሲለደስ ንጉስ ትዕዛዝ ሃይማኖት እንደቀድሞዋ ሆነች የሮም ሃይማኖትም ፈለሰች በማለት ያስረዳል።
ከዚህ ሁሉ በኋላ አባታችን አቡነ ሐራ ድንግልም ወደ እርሳቸው ከመጡ መነኮሳት ጋር ተሰብስበው ወደ ቅዱስ ሚናስ ቤተ-ክርስቲያን ሄደው በመፀለይ ለ 17 ዓመት ተዘግቶ የነበረ ቤተ-ክርስቲያን ተከፈተላቸው። በአንድነትም ቆሙ በማህሌትና በእልልታ በከበሮና በጸናጽንም አመስግነው የጌታችንና የመድሓኒታችንን ቅዱስ ስጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለው ወደ በዓታቸው እንደተመለሱ ገድለ አቡነ ሐራ ድንግል ይናገራል።
ቅዱሱ አባታችን አቡነ ሐራ ድንግል ከአረፉ በኋላ ግን ይህ ቤተክርስቲያን ሰው በማጣት ጠፍ የአራዊት መኖሪያ ሆኖ ለ 400 ዓመት እንደቆየ አባቶች ይናገራሉ። ምንም እንኳን ይህ ቦታ የአራዊት መኖሪያ ቢሆንም ቅዱሳን ግን እንዳልተለዩት የአካባቢው ነዋሪዎችና የቀደሙ አባቶች ይናገራሉ። የቤተክርስቲያን ደወል እና የእጣን መዓዛ ይሸታቸው እንደነበርም ይመሰክራሉ።
የእግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖ ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት በአቡነ ሐራ ድንግል ገዳም እገዛ እና በአካባቢው ነዋሪዎች ትብብር ዛሬ ያለው መቃረቢያ (መቃኞ) ተሰርቶ ታቦቱ ለመግባት ችሏል።
የቅዱስ ሚናስ ዓመታዊ በዓሉ ህዳር ፲፭ ቀን በድምቀት ይከበራል።  የሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ በረከት እና ረድኤት አይለየን

1 comment:

  1. kale hiwotin yasemalin berta wondimachin....

    ReplyDelete